ኮቪድ-19 እና አርሶ አደሮች፡- የወረርሽኙ ምላሽ በገጠራማው ርዋንዳ

Script

Save and edit this resource as a Word document

መግቢያ

ርዋንዳ የቆዳ ስፋቷ 26,000 ካሬ ኪሎሜትር ሲሆን በአፍሪካ ካሉ በጣም ትናንሽ አገሮች አንዷ ናት፡፡ በንጽጽር ጎረቤቷ ታንዛንያ 35 እጥፍ ትሰፋለች፡፡ ርዋንዳ ከዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ እና ታንዛኒያ ጋር ትዋሰናለች፡፡ ሃገሪቱ ተራራማና መልክአምድር እና ለም አፈር ያላት ስትሆን፣ ኢኮኖሚዋ በዋናነት ከአጅ ወደ አፍ በሆነ ግብርና ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ዘጠና በመቶ የሚሆነው ሕዝቧ ከግብርና ጋር ተዛማጅ በሆኑ ሥራዎች ውስጥ ያለ ሲሆን የግብርና አስተዋጽኦ ለአጠቃላይ ሃገራዊ ምርት በ2010 አና በ2019 ዓም 42 በመቶ እና 29 በመቶ ነበር፡፡

በ1994 ዓም በቱትሲ ብሄረሰቦች ላይ የተደረገው ዘር ማጥፋት ሃገሪቱን አሽመድምዷት የነበረ ሲሆን ከዚህ የባህር በር ከሌላት ሃገር ታምር ይፈጠራል ብሎ ጠበቀ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከዚያ ወዲህ ርዋንዳ አገልግሎት፣ መሰረተ ልማት፣ ትምህርት እና ያልተማከለ ጤና አገልግሎት እና አስተዳደር ላይ ያለ ማቋረጥ መዋዕለ ንዋይ አፍስሳለች፡፡ ይህም ሃገሪቱን የሁሉን አቀፍ የጤና ሽፋን ለማሳካት እንድትቃረብ አስችሏታል፡፡ ሰማንያ አምስት በመቶ የሚሆነው ሕዝብ ሰፊ ትስስር ላለው ጥራቱን የጠበቀ የጤና አገልገሎት ተደራሽ ነው፡፡ እንደ ኮቪድ-19 ላሉ የጤና ስጋቶች መንግስት ለሚያወጣቸው የተግባቦት እቅዶች ባካባቢቸው ባሉ ማሕበረሰቦች ውስጥ ለስጋት ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለይተው የሚያውቁት አካባቢያዊ ባለስልጣኖች እና መሪዎች ቁልፍ ሚና አላቸው፡፡

የሃብት ችግር ካለባቸው ሌሎች የአፍሪካ የጤና ስርኣቶች ጋር ሲነጻጸር ያልተማከለ የሪፈራል ስርኣት ያላት ርዋንዳ የተሻለ ረብ አላት፡፡ በከተማም ሆነ ሩቅ እና ገጠራማ አካባቢዎች ሁሉ በአካባቢ እና በማሕበረሰብ ደረጃ እንደ ወረርሽኝ ያሉ የጤና ስጋቶች በዝቅተኛው የስርአቱ ደረጃዎቸ የቁጥጥር ስራ ይደረግባቸዋል፡፡ ለሁሉም የገጠርና ግብርና ማሕበረሰቦች ተደራሽነት ያላቸው ሕዋስ በመባል ከሚታወቅ ዝቅተኛው የጤና አካል እስከ ማሕበረሰብ ጤና ሠራኞች ድረስ በገጠር እና በግብርና አካባቢዎች ያሉ ግለሰቦች ከቤታቸው በአንድ ማይል (1.66ኪሜ) ርቀት ውስጥ የህክምና አገልግሎት ማግኘት ይችላሉ፡፡ ሕዋሶቹ የመጀመርያው የአገልግሎት እርከን ሲሆኑ ከ2,500 በላይ የሚሆኑ ጤና ኬላዎች በገጠር እና በሩቅ ቦታዎች በሽተኞችን በየቀኑ ይቀበላሉ፡፡ ጤና ጣቢያዎች ሕዝብ ቁጥር ከፍ በሚልባቸው ቦታዎች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ ሕክምና አገልገሎት ከሚሰጡ ጤና ጣቢያዎች ሰዎች ወደ ዲስትሪክት ሆስፒታሎች ሪፈር ይደረጋሉ፡፡

ርዋንዳ ለኮቪድ-19 ምላሽ በመስጠት እና ወረርሽኙን በመቆጣጠር ጥሩ ግስጋሴ አሳይታለች፡፡ኮቪድ-19ን በመቆጣጠር ያሳየችው ስኬት በዋናነት ያልተማከለ የጤና ስርኣቷ፣ የመንግስት የቅኝት ሥራ እና በብሔራዊ ኢጀንሲዎች (ለምሳሌ ጤና ሚኒስቴር፣ የርዋንዳ ባዮሜዲካል ማዕከል፣ ብሐራዊ ፖሊስ እና መከላከያ ኃይል) እና የአካባቢ መንግስታት መካከል ያለ ትብብር ውጤት ነው፡፡ የመጀመርያ ጤና ክብካቤ የመስጠት ልምድ ያላቸው በብሔራዊ ደረጃ እና ባልተማከሉ የመንደር ደረጃዎች ላይ ያሉ የማህበረሰብ ጤና ሠራተኞች ኮቪድ-19ን ለመከላከል እንዲንቀሳቀሱ ተደርጓል፡፡ ሌላው ለስኬት አስተዋጽኦ ያደረገው ርዋንዳ ኢቦላ ቫይረስን ለመከላከል ባደረገችው ምላሽ የሪፖርት ስርኣት እና የእጅ መታጠብ ልምድ አስቀድማ ያካበተች መሆኗ ነው፡፡

ኮቪድ-19 በርዋንዳ፡- የጊዜ ተዋረድ

የመጀመርያው የኮቪድ-19 በሽተኛ መጋቢት 5፣ 2012 ፖዘቲቭ ከሆነ በኋላ የርዋንዳ መንግስት በቅርብ ግንኙነት የነበራቸውን ሰዎች የማሰስ* እና የመወሸብ* እርምጃዎችን ጨምሮ እንቅስቃሴ መገደብ ጀመረ፡፡ የጤና ባለስልጣናት ግንዛቤ ለማሳደግ ከህዝቡ ጋር በተለያዩ መንገዶች የተግባቦት ሥራ የሠሩ ሲሆን ከነዚህም መካከል የማሕበራዊ ሜዲያ፣ የጤና ሚኒስቴርን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት አካላት ድረ ገጾች፣ ቴሌቪዝን፣ ራዲዮ፣ የሞባይል የጽሑፍ መልእክት እና ቲያትራዊ ድራማዎች ይገኙበታል፡፡ በእነዚህ መንገዶች ለሕዝቡ አዳዲስ የኮቪድ-19 ለውጦችን መረጃ መስጠት እና እጅን ከመታጠብ፣ ብዙ ሰው የተሰበሰበባቸውን አካባቢዎች መራቅ፣ አካላዊ እርቀትን መጠበቅ፣ ክፍያን ከጥሬ ገንዘብ ውጪ ማበረታታት እና የበሽታውን ምልክቶች በነጻ የስልክ መስመር ማሳወቅ የመሳሰሉትን የጥንቃቄ እርምጃዎች የማሳወቅ ሥራ ተሠርቷል፡፡ ባጭር ጊዜ ውስጥ የእጅ መታጠቢያ ቧንቧዎች በዋና ከተማዋ ኪጋሊ እና በገጠራማ አካባቢዎች ሁሉ የአውቶብስ መቆሚያዎች፣ የገበያ ቦታዎች፣ የንግድ ድርጅቶች እና ሕንጻዎች ላይ ተገጥመው ነበር፡፡

ከሰባት ቀነ በኋላ የኮቪድ-19ን ስርጭት ለመገደብ የሁለት ሳምንት የእንቅስቃሴ እገዳ በአገሪቱ ዙርያ ተጣለ፡፡ በዚያን ጊዜ ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች 17 ብቻ ነበሩ፡፡ አላስፈላጊ የሆኑ እንቅስቃሴዎች ታገዱ፣ የትምህርት ቤቶች እና ዩኒቨርስቲዎች ትምህርት ተቋረጠ፣ እና ስብሰባዎች ተከለከሉ፡፡ ሕዝቡ የተገናኟቸውን ሰዎች ለማሰስ የሚሆን ትክክለኛ መረጃ እንዲሰጡ ያ ሳይሆን ቢቀር ቅጣት እንደሚኖር ማስጠንቀቂያ ተሰጠ፡፡ የርዋንዳ ፖሊስ በሰኣት እላፊ፣ የገንዘብ ቅጣት እና አጭር እስር የመሳሰሉ ሌሎች እርምጃዎች አማካኝነት መመርያዎችን ማስፈጸም ጀመረ፡፡ ሰፊ የቅኝት ሥራም ነበር፤ የመንግስት መመርያዎች እንደተጣሱ ሲጠረጥሩ ሰዎች በየራሳቸው ላይ ሳቀር መረጃ ለመንግስት ያቀርቡ ነበር፡፡

በተጨማሪም የሕክምና እቃዎች አቅርቦት እንዳይስተጓጎል መንግስት ፋርማሲዎችን የሳኒታይዘር እና ፓራሲታሞል (አሲታሚኖፌን) ዋጋ እንዳይ ጨምሩ ቢጨምሩ እንደሚቀጡ አዘዘ፡፡

በኮሮናቫይረስ ፍርሃት ምክንያት መሰረታዊ የምግብ እቃዎች ዋጋ በአፍሪካ ዙርያ ሲጨምር፣ ሸማቾች ወሳኝ ሸቀጦችን ማጠራቀም ሲጀምሩ እና ሻጮችም ትርፍ ለማግኘት ሲሞክሩ በነበረበት ወቅት የርዋንዳ መንግስት በመጋቢት እንቅስቃሴን ሙሉ በሙሉ በመገደብ እና የሃገሪቱን ድንበርም በመዝጋት በአፍሪካ የመጀመርያው ነበር፡፡ ለጉዳት ተጋላጭ ለሆኑ ቤተሰቦች መንግስት በሃገሪቱ ዙርያ ምግብ ያከፋፍል ነበር፡፡ በመጋቢት ወር ውስጥ ሩዝ፣ ፓስታ፣ የበቆሎ ዱቄት፣ ባቄላ፣ ሳሙና፣ የምግብ ዘይት እና የገንፎ ዱቄትን ጨምሮ የ17 ወሳኝ ሸቀጦችን ዋጋ መንግስት ወስኖ ነበር፡፡ ይህንን ሂደት ይመሩት የነበሩ በሕዋስ እና በመንደር ደረጃ ያሉ የአካባቢ መሪዎች ነበሩ፡፡ መንግስት በተጨማሪ በብዛት ከቻይና የሚገቡ የተቀነባበሩ ምግቦችን ዋጋም ወስኖ ነበር፡፡

በመንግስት ምግብ ስርጭት እና ዋጋ ውሰና ሥራ ዋና ተጠቃሚ የነበሩት ለጉዳት ተጋላጭ የነበሩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ነበሩ፤ እነዚህም ስራቸውን ያጡ ሰዎች እና በእለት ገቢ የሚተዳደሩ፣ ኢመደበኛ በሆነው ዘርፍ በግንበኝነት፣ በጸጉር ቤት፣ በሞተር ሳይክል ታክሲ ሾፌርነት፣ በመጠጥ ቤቶች እና በቀን ሥራ የተሰማሩ ሰዎች ናቸው፡፡

የኮቪድ-19ን ስርጭት ለመግታት አገር አቀፉ የእንቅስቀሴ እገዳ ከመጋቢት 12 በኋላ ተራዝሞ ነበር፡፡ እገዳው ሲቀጥል ግን በተለይ በከብት እና ዶሮ እርባታ ሥራ የተሠማሩ በርካታ አርሶ አደሮች ተግዳሮት አጋጠማቸው፡፡ በግንቦት 2012 ምርቶቻቸውን የሚያሰራጩበት መስመር በኮሮናቫይረስ እንቅስቃሴ እገዳ የተነሳ ተቋርጦ ነበር፡፡

መንግስት መመርያዎቹ መጠበቃቸውን ለማረጋገጥ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን ተጠቅሟል፡፡ ኪጋሊ ውስጥ ወሼባ ውስጥ ለነበሩ ሰዎች ምግብ እና መድሃኒት በሮቦት አማካኝነት ይቀርብ የነበረ ሲሆን፤ እነዚህ ሮቦቶች የኮቪድ-19 ፍተሻ ምርመራ ያካሂዱና ውጤቱን ለጤና ሠራተኞች ያስታላልፉ ነበር፡፡ እገዳውን የሚጥሱ ሰዎችን ለመቆጣጠር እና ለማሰስ ድሮኖች ሥራ ላይ ውለው ነበር፡፡ በሐምሌ ደግሞ የጤና ሚንስቴር በቀን 5,000 ሾፌሮችን፣ እግረኞችን እና የሞተርሳይክል ታክሲ ሾፌሮችን በኪጋሊ እና የሃገሪቱ ድንበር ጣቢያዎች ላይ መመርመር ጀመረ፡፡

ኮቪድ-19 በቁጥር

እስከ መስከረም 22፣ 2013 ርዋንዳ በኮቪድ-19 ዓለም አቀፍ ደረጃዋ 136ኛ የነበረ ሲሆን 5,060 የተረጋገጡ በበሽታው የተያዙ ሰዎች የነበሩ ሲሆን ከእኒዚህም ውስጥ 4,806 ያገገሙ ሲሆን 220 ደግሞ ጽኑ ሕክምና ላይ ነበሩ፡፡ በሽታው በመጋቢት 2012 ከተመዘገበ ወዲህ ሰላሳ አራት ሰዎች ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡

እስከ ፈረንጆቹ ሰኔ መጀመርያ ድረስ በሳምንት ባማካኝ 36 ተጨማሪ ሰዎች በበሽታው ይያዙ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ሳምንታዊ አማካኙ 284 ደርሷል፡፡ አጠቃላይ የሟቾች ቁጥርም ከሦስት ወደ 34 በመጨመር ተመሳሳይ ለውጥ አሳይቷል፡፡

በችኮላ ሲታይ ይህ ቁጥር አስደንጋጭ ወይም የወረርሽኙ ቁጥጥር ሥራ የከሸፈ ሊያስመስል ይችላል፡፡ በቅርብ ሲመረመር ግን ርዋንዳ ወረርሽኙን በመቆጣጠር ስኬት ካስመዘገቡ አገሮች ውስጥ መሆኗን ያሳያል፡፡

ለያንዳንዱ ሚሊዮን ሕዝብ በርዋንዳ 388 ሰዎች በቫይረሱ ሲያዙ 3 ሰዎች ደግሞ ይሞታሉ – ሁለቱም በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲታዩ ዝቅተኛ ቁጥሮች ናቸው፡፡ የሟቾች ቁጥር ዝቅተኛ መሆኑና የሚያገግሙት ሰዎች ቁጥር ከፍተኛ መሆን ዉጤታማ የወረርሽኝ ቁጠጥር ሥራን እና በርዋንዳ ያለው ከፍተኛ የጤና ሽፋን ያመጣውን አዎንታዊ ተጽእኖ ያሳያል፡፡

በቅርብ እየታየ ያለው በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር መጨመር በእርግጠኝነት የምርመራ ቁጥር ከመጨመሩ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሃገሪቱ በቫይረሱ የተያዘው የመጀመርያው ሰው ከመገኘቱ በፊት ጀምሮ ሲሆን ምርመራ የጀመረችው እለታዊ የምርመራ አቅሟ በሚያዚያ ከነበረው 891 ተነስቶ አሁን 2,421 ደርሷል፡፡ የፈረንጆች ነሐሴ መጨረሻ ላይ እለታዊ ምርመራ 5,382 ደርሶ ነበር፡፡ የቅርብ ንክኪ የነበራቸው ሰዎች በማሰስ የሚደረገው ምርመራ ቁጥራቸው አነስተኛ የሆኑ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን እየሰጠ ስለነበር አሁን ወዳለበት ቁጥር ዝቅ ብሏል፡፡ በንጽጽር የዩኬ መንግስት በቀን 270,000፣ የኮርያ 9,000 እየመረመሩ ሲሆን ጀርመን “መርምር፣ አድን፤ ለይ” በሚለው ጠንካራ አሠራር በሳምንት አንድ ሚሊዮን ምርመራዎችን ታካሂዳለች፡፡ እስከ ጥቅምት 15፣ 2012 ዓም ድረስ ርዋንዳ ከግማሽ በላይ ምርመራዎችን አካሂዳ የነበረ ሲሆን ይህም በሚሊዮን ሕዝብ 41,000 ምርመራዎችን በማከናወን በአፍሪካ 12ኛ ደረጃ ላይ ያስቀምጣታል፡፡

ቫይረሱ ያለባቸው ሰዎች ቁጥር ከጨመረባቸው ሌሎች ምክንያቶች ውስጥም ተጨማሪ ጥናት ቢያስፈልግም የእንቅስቃሴው እገዳ መነሳት ፣ የንግድ እንቅስቃሴ መጀመር እና የድንበር መከፈት ሊሆን ይችላል፡፡

ሃገሪቱ ከጎረቤት ሃገሮች ጋር በመተባበር 1,900 አሳሾችን በመመደብ በገጠራማ አካባቢዎች የቅርብ ግንኑነት የነበራቸው ሰዎችን አሰሳ ለመተግበር እቅድ አላት፡፡

በአጭሩ ለኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምላሽ በመስጠት ርዋንዳ ምሳሌነት ካላቸው አገሮች ውስጥ ትመደባለች፡፡

የርዋንዳ አርሶ አደሮች ለኮቪድ-19፣ ከባድ ዝናብ እና ጎርፍ ያገኙት ድጋፍ

አርሶ አደሮች የእርሻ ሥራቸውን እንዲቀጥሉ ተፈቅዶላቸው ስለነበር ከኢኮኖሚያዊ ኪሳራ እና የምግብ ተደራሽነት ችግር አንጻር ገጠራማ አካባቢዎች በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሳቢያ ብዙም አልተጎዱም ነበር፡፡ ነገር ግን በሚያዚያ እና ግንቦት የነበረው ዝናብ መጠነ ሰፊ የመሬት መንሸራተት እና ጎርፍ አደጋዎችን አስከትሎ ነበር፡፡ በዚህም የተነሳ መተዳደርያ ሥራዎች፣ ግብርና፣ መጠለያ፣ መሰረተ ልማት እና አከባቢ ላይ እንዲሁም ገቢ ማግኛ እንቅስቃሴዎች ላይ ተጽእኖ ተፈጥሮ ነበር፡፡ በዋናነት ለጉዳት የተጋለጡት በሰሜናማው የሃገሪቱ ክፍል የሚገኘቡት ኒያቢሁ፣ ሩባቩ እና ጋኬንኬ ነበሩ፡፡

መጋቢት 2012 ድረስ በነበረው የሰብል ወቅት ከአማካኝ በላይ የሆነ ምርት አግኝተው ስለነበርና ከግንቦት እስከ ሃምሌ ድረስ መደበኛ ምርት ለማግኘት ጠብቀው ስለነበር ጎርፉ እስከሚመጣ ድረስ አርሶ አደሮች ከራሳቸው ምርት የተሻለ የምግብ አቅርቦት ጠብቀው ነበር፡፡

የምግብ እና ግብርና ድርጅት (ፋኦ) ከአለም አቀፍ ስደት ድርጅት (አይኦኤም) እና ሌሎች አጋሮች ጋር በመሆን ከመስከረም 29፣ 2012 ዓም አስቸኳይ የግብርና ግብኣቶች እና መሣርያዎችን በጎርፍ ለተጎዱ ሰዎች ማቅረብ ጀምሯል፡፡ አይኦኤም ቤታቸው በዝናብ ለፈረሳባቸው ለጉዳት የተጋለጡ ቤተሰቦች መጠለያ አቅርቧል፡፡ ከድጋፉ ተጠቃሚ ከሆኑ ቤተሰቦች መካከል እማወራዎች፣ አረጋውያን፣ እርጉዝ እና የሚያጠቡ እናቶች፣ ሕጻናት እና አካል ጉዳተኞች ይገኙበታል፡፡ የተለያዩ ሰብሎች በየበቀሉበት እርሻዎቻቸው በጎርፍ የወደሙባቸው ለጉዳት ተጋላጭ ግለሰቦች በብረት የበለጸገ ባቄላ፣ ድቃይ በቆሎ፣ ማዳበርያ እና የግብርና መሣርያዎች ተቀብለዋል፡፡

አካላዊ እርቀትን እና ሌሎች የጥንቃቄ እርምጃዎችን መከተል ጋር የተያያዙ ችግሮች

በርዋንዳ ምስራቃዊ ክፍል የሚገኘው ኒያጋታሬ ዲስትሪክት በሃገሪቱ ትልቁ እና በሕዝብ ብዛት አንደኛ የሆነ ግዛት ነው፡፡ ዲስትሪክቱ ከፍተኛ የከብቶች ቁጥር ያለው ሲሆን መሬቱ እንደሌሎች የሃገሪቱ ክፍሎች በስፋት አልታረሰም፤ ይህም የኮቪድ-19 ስርጭትን ስጋት እና ጥብቅ ማሕበራዊ መራራቅን አስፈላጊነት ሊቀንስ ይችላል፡፡

በነሃሴ 2020 ከአካባቢው አትክልት አብቃዮች ጋር ለመነጋር ተጉዞ የነበረ አንድ የተባበሩት መንግስታት ሠራተኛ በአካባቢው ያሉ አርሶአደሮች የኮቪድ-19 መከላከያ መንገዶችን ምን ያህል እንደተገነዘቡ ሪፖርት አቅርቦ ነበር፡፡ አካላዊ እርቀትን መጠበቅ፣ ማስክ መጠቀም እና የእጅ ንጽህናን መጠበቅ በተመለከተ አርሶ አደሮች እነዚህን መከላከያ መንገዶች ለመተግበር አስቸጋሪ በሆኑ ቦዎች ሁሉ ሳይቀር አርሶ አደሮች እጃቸውን በተደጋጋሚ ይታጠቡ እና ሳኒታይዘር ይጠቀሙ እንደነበር ታዝቧል፤ በቤታቸው ወይም የአካባቢው ባለስልጣናት በገጠሙላቸው ቧንቧዎች በመጠቀም እየታጠቡ እንደነበር ግን ግልጽ አይደለም፡፡ አርሶ አደሮች ከምሽቱ 4-5 ሰዓት የተጣለውን ሰዓት እላፊም እያከበሩ ነበር፡፡

በኒያጋታሬ የሕዝብ መጨናነቅ ቢኖርም እጅን መታጠብ እና ሰዓት እላፊውን ማክበር ሳይጠቅም አልቀረም፣ ምክንያቱም ምንም የተመዘገበ የኮቪድ-19 ኬዝ የለም፣ ከኮቪድ-19 ምልክቶች ጋር በተያያዘም ለይቶ ማቆያ ውስጥ የገባ ሰው የለም፡፡ ርዋንዳ ለኢቦላ ሕክምና የተቋቋሙ እና ሌሎች መሰል አስቀድመው የተቋቋሙ ተቋማትን በመጠቀም ፋንታ ለኮቪድ-19 ልዩ የሕክምና እና የለይቶ ማቆያ ማእከላትን አዘጋጅታለች፡፡

የጉዞ እና የእንቅስቃሴ ግደባዎች እና ሌሎች እርምጃዎች አርሶ አደሮች ላይ የተለያዩ ተጽእኖዎችን ፈጥረዋል፡፡ አንዳንድ አርሶ አደሮች የግብርና ሥራቸውን ለማሻሻል ይጠቀሙበት የነበረውን ገንዘብ ቤተሰቦቻቸው ለአስቸኳይ ፍላጎቶቻቸው እና መሠረታዊ ጤናቸውን ለመጠበቅ እንዲጠቀሙበት አውለውታል፡፡

ሸቀጦችን ማጓጓዝ እና ደምበኞቻቸው ጋር ቶሎ ቶሎ ለመገናኘት አስቸጋሪ ነው፤ አዳዲስ ደምበኞችን ማፍራት የሚቻልም አይደለም፡፡ አንድ አርሶ አደር መደበኛ ደምበኞቹን መጠበቅ ትቶ ምርቶቹን ወደ ኪጋሊ እየሄደ እንደሚሸጥ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን አርሶ አደሩ ወደ ኪጋሊም መሄድ አልቻለም፣ ምርቶቹንም ለነባር ደምበኞቹ ማድረስ አልቻለም፡፡ በተለምዶ በዚህ አካባቢ በሄክታር አምስት ቶን አከባባቢ ፍራፍሬ እና አትክልት የሚመረት ሲሆን አሁን ግን ወደ ሦስት ቶን ወርዷል፣ ቀሪው ምርት ይበላሻል፡፡

የርዋንዳ አርሶ አደሮች ድጋፍ ከመንግስት እና የተለያዩ የዩኤን ፕሮግራሞች በተጨማሪ ከኡቡዴሄም ያገኛሉ፡፡ ኡቡዴሄ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ማሕበሰባዊ ችግሮችን ለመፍታት ማህበራዊ ሥራዎች፣ እንክብካቤ እና የጋራ ድጋፍ የሚደረግበት ልማድ ነው፡፡ ብዙ የአርሶ አደሮች የሕብረት ሥራ ማህበራት እና ግለሰብ አባላት በኮቪድ-19 እንቅስቃሴ እግድ የተነሳ ለተጎዱ ወገኖቻቸው የምግብ እርዳታ አቅርበዋል፡፡ ለምሳሌ በምስራቃዊ ርዋንዳ ካቢያኪ የግብርና ህብረት ሥራ ማሕበር እና በአቅራቢያው ያለው የቱዛሙራኔ-ሲየዛ ሕብረተሰብ በሕብረት ሥራ ማህበራቱ የተመረተ አንድ ቶን በቆሎ እና ሌሎች የምግብ ሸቀጣሸቀጦችን በ42 አባወራዎች ውስጥ ለሚኖሩ 200 ሰዎች ለግሰዋል፡፡ እያንዳንዱ ቤተሰብ 20 ኪሎ በቆሎ፣ አምስት ኪሎ ሩዝ፣ ለሕጻናት የሚሆን ሁለት ኪሎ የገንፎ እህል፣ አንድ ሊትር ዘይት እና አንድ ሳሙና ተቀብሏል፡፡

የርዋንዳ የገጠር ሴቶች በግብርና ሥራ ውስጥ በአምራችነት፣ በአቀነባባሪነት፣ ወደ ገበያ በማቅረብ እና በኢመደበኛ ነጋዴነት ሙሉ ተሳትፎ ያደርጋሉ – እነዚህ እንቅስቃሴዎቻቸው ግን በችግሩ የተነሳ በከባድ ሁኔታ ተገድበውባቸዋል፡፡ በጉዞ ክልከላዎች እና እየተባባሰ በመጣው ሥራ አጥነት ምክንያት የሴቶች ገቢ የማግኘትእድሎች መመናመን በቤት ውስጥ ያላቸው የመወሰን አቅም ላይ ተጽእኖ በማሳደር የቤት ውስጥ የስነምግብ እና መልሶ ማገገም አቅም ላይ ጉዳት ያደርሳል፡፡

ጾታዊ ጥቃት ኮቪድ-19ን እንደ ጥላ የሚከተል (a “shadow pandemic”) ወረርሽኝ ተብሏል፡፡ ዩኤን ዊመን እንደሚናገረው በአፍሪካና በሌሎቸ የአለም ክፍሎች የቤት ውስጥ ጥቃት ነጻ የስልክ መስመሮች እና መጠለያዎች እየጨመረ የመጣ የድረሱልኝ ጥሪዎችን እያስተናገዱ ነው፡፡ በአለም ጤና ድርጅት መረጃ መሰረት የኮቪድ-19 እንቅስቃሴ ግደባዎች እና ኢኮኖሚያዊ ጥርጣሬዎች የፈጠሩት ጭንቀት ኃይለኛ ጥቃቶችን እያባባሰ ነው፡፡ ወረረሽኙ ጥቃት ባለበት ግንኙነት ውሥጥ ያሉ ሴቶችን ከአጥቂዎቻቸው ጋር ቤት ውስጥ አብረው እንዲቆዩ አስገድዷቸዋል፡፡

በርዋንዳ የታየው አንዱ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ አወንታዊ ተጽእኖ ሃገሪቱ በገጠራማ አካባቢዎች ጾታዊ ጥቃት ላይ እንድታተኩር እና እና ጾታዊ እኩልትን እንድታራምድ አድርጓታል፡፡ በካሲዪሩ ፖሊስ ሆስፒታል የተቋቋመው የኢሳንጌ One Stop Center ከጾታዊ ጥቃት የተረፉ ሰዎች መሰብሰቢያ ሆኗል፡፡ ከጥቃት የተረፉ ሰዎች በማዕከሉ ሁሉንም አገልግሎት በአንድ ቦታና በነጻ ማግኘት ይችላሉ፡፡ የሃገሪቱ የጾታና ቤተሰብ ማስፋፍያ፣ የጤና እና የፍትህ ሚኒስቴር መሥርያ ቤቶች ከርዋንዳ ብሔራዊ ፖሊስ ጋር በመሆን ማዕከሉን ያንቀሳቅሳሉ፡፡ እንቅስቃሴዎች በ2001 ዓም (2009እኤአ) በሙከራ ደረጃ ጀምሮ አሁን በሁሉም ዲስትሪክቶች እየተተገበረ ነው፡፡ አሁን ርዋንዳ በሁሉም ዲስትሪክቶች One Stop Centre አላት፡፡ ማእከሉ በየቀኑ እስከ 12 የሚደርሱ ከጥቃት የተረፉ ሴቶችን ይቀበላል፡፡

ሴቶች የሚያገኙት ገቢ ወደ ትምህርት፣ ጤና ክብካቤ፣ እና የሴቶች ግብርና ሥራዎች ወይም የሥራ ፈጠራዎች ላይ ስለሚውሉ የሴቶች የመተዳደርያ እድሎች ሲቀንሱ ሌሎች ተከታይ ተጽእኖቸዎች ይኖራሉ፡፡ በርዋንዳ የኮቪድ-19ን ጾታዊ ተጽእኖዎች ዳግም መመርመር እና የሴቶች ማጎልበትን ማካተት ለድህረ ኮቪድ-19 የመልሶ ማንሰራራት እና ማገገም ስትራቴጂዎች ወሳኝ ነው፡፡

ርዋንዳ አለም አቀፉን ወረርሽኝ የመቆጣጠር ስኬቷን በሳይንስ ላይ የተመሰረቱ ፖሊሲዎችን እና ቴክኖሎጂዎችን በመተግበር ጀመረች፡፡ ርዋንዳ ለሌሎች ሃገሮች በተለይ በአፍሪካ ላሉት የሚከተሉት ምሳሌ አስቀምጣላቸዋለች፡፡ አሁን ጥያቄው ከነሃሴ ሰባት ጀምራ ኤርፖርቶቿን ስትከፍት ወደ ምስራቅ አፍሪካዊቷ ሃገር የሚገቡት ሰዎች ከኮቪድ-19 ነጻ መሆናቸውን ማረጋገጥ ትችላች ወይ የሚለው ነው፡፡

እንደሌሎች የአፍሪካ ሃገራት ሁሉ ርዋንዳም ከውጭ የሚመጡ ተጓዦች ከኮቪድ-19 ነጻ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ሰርቲፊኬት ይዘው እንዲመጡ ትጠይቃለች፡፡ በተጨማሪም ተጓዦች እንደደረሱ ምርመራ ተደርጎላቸው የምርመራው ውጤት እስከሚደርስ ድረስ ቢያንስ ለ24 ሰዓት ራሳቸውን መለየት አለባቸው፡፡ እነዚህ እርምጃዎች ምን ያህል ስኬታማ አንደሚሆኑ ገና ግልጽ አይደለም፤ እንደተሳካላት ከሚያሳዩት ማመልከቻዎች አንዱ ግን ርዋንዳ በአውሮፓ ሕብረት ምክርቤት የተላላፊ በሽታ ስጋት የሌለባቸው ተብለው በዓለም ዙርያ ከተመረጡ 11 ሃገራት ውስጥ አንዷ መሆኗ ነው፡፡

ቁልፍ ትርጉሞች

Contact tracing: ሦስት መሰረታዊ ደረጃዎች ያሉት የቁጥጥር ሂደት ነው – ግንኙነት የነበራቸው ሰዎችን መለየት፣ ግንኙነት የነበራቸውን ሰዎች መዘርዘር፣ እና ግንኙነት የነበራውን ሰዎች ክትትል ማድረግ፡፡

Isolation: ተላላፊ በሽታ ያለባቸውን ሰዎች ካልታመሙት ሰዎች መለየት፡፡

Quarantining: ለተላላፊ በሽታ የተጋለጡ ሰዎችን በሽታው ይታይባቸው እንደሆነ ለማየት መለየት እና እንቅስቀሴያቸውን መገደብ፡፡

Universal Health Coverage (UHC): ሁሉም ሰዎች ውጤታማ ለመሆን በቂ ጥራት እና ይህንን አገልግሎት ሲያቀርብ የገንዘብ ችግር የማያስከትል የአስፈላጊ የሕክምና አገልክሎቶች ተደራሽነት ሲኖራቸው የሚፈጠረው ሁኔታ – ይህም መከላከል፣ ማስፋፋት፣ ሕክምና፣ ወደ ነበሩበት መመለስ እና የህመም መቆጣጠርን ይጭመራል፡፡

 

Acknowledgements

ምስጋና

የጽሑፉ አዘጋጅ፡- ኤሊዛቤት ውልሰን፣ ጋዜጠኛ እና የተግባቦት ስፔሻሊሰት

ይህ ጽሑፍ በግሎባ አፌይርስ ካናዳ አማካንነት ከካናዳ መንግስት በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ተዘጋጀ፡፡

Information sources

የመረጃ ምንጮች:-

  1. Adepoju, P., 2020. Gender-based violence – the “Shadow Pandemic” of COVID-19. Health Policy Watch. https://healthpolicy-watch.news/75409-2/
  2. Baryio, N., 2020. Rwanda’s aggressive approach to Covid wins plaudit – and warnings. The Wall Street Journal. https://www.wsj.com/articles/rwandas-aggressive-approach-to-covid-wins-plauditsand-warnings-11601372482
  3. Beaubien, J., 2020. Why Rwanda is doing better than Ohio when it comes to controlling COVID-19. NPR. https://www.npr.org/sections/goatsandsoda/2020/07/15/889802561/a-covid-19-success-story-in-rwanda-free-testing-robot-
  4. Bishumba N., 2020. 8 things you need to know about gov’t food distribution programme. New Times. https://www.newtimes.co.rw/news/8-things-you-need-know-about-govt-food-distribution-programme
  5. Dayton, K., and Williamson, J., 2020. Women’s empowerment in agriculture is essential to COVID-19 survival and recovery. Agrilinks. https://www.agrilinks.org/post/womens-empowerment-agriculture-essential-covid-19-survival-and-recovery
  6. Devlin, H., 2020. Is 100.000 tests a day an effective strategy against coronavirus? The Guardian. https://www.theguardian.com/world/2020/may/01/is-100000-tests-a-day-an-effective-strategy-coronavirus
  7. Isaac, K, 2020. How Rwanda plans to save farmers from effects of COVID-19. Taarifa. https://taarifa.rw/how-rwanda-plans-to-save-farmers-from-effects-of-covid-19/
  8. Kagire, E., 2020. Rwanda: How COVID-19 relief distribution will work. KT Press https://www.ktpress.rw/2020/03/rwanda-how-covid-19-relief-distribution-will-work/
  9. Kripahl, C., 2020. Price hikes in Africa aggravate the coronavirus crisis. Deutsche Welle. https://www.dw.com/en/price-hikes-in-africa-aggravate-the-coronavirus-crisis/a-52820553
  10. Kuteesa, H., 2020. Rwanda: Govt extends lockdown until April 30. https://allafrica.com/stories/202004200427.html
  11. Maema, C., 2020. Rwanda to conduct street testing survey of COVID-19 in capital city. CGTN Africa. https://africa.cgtn.com/2020/07/02/rwanda-to-conduct-street-testing-survey-of-covid-19-in-capital-city/
  12. Nohana online journal, 2020. FAO has provided emergency agricultural support to disaster victims in Rwanda. http://nonaha.com/fao-has-provided-emergency-agriculture-support-to-disaster-victims-in-rwanda
  13. Nshiyimana, P., 2020. Rwanda controls COVID-19, but its farmers still struggle. Cornell Alliance For Science. https://allianceforscience.cornell.edu/blog/2020/08/rwanda-controls-covid-19-but-its-farmers-still-struggle/
  14. Our World in Data, 2020. Rwanda: Coronavirus Pandemic Country Profile. https://ourworldindata.org/coronavirus/country/rwanda?country=~RWA
  15. Rwibasira E., 2020. Effects of COVID-19 on farming in Rwanda: the fate of poultry farming. The New Times. https://www.msn.com/en-za/news/other/effects-of-covid-19-on-farming-in-rwanda-the-fate-of-poultry-farming/ar-BB13u99Q
  16. Schengen Visa Info, 2020. EU’s list of epidemiologically safe countries amid Covid-19.
    https://www.schengenvisainfo.com/eu-list-of-epidemiologically-safe-countries-amid-covid-19/
  17. Ssebwami, J., 2020. COVID19 crisis: Rwanda begins distribution of essential goods to citizens affected by coronavirus lockdown. PML Daily. https://www.pmldaily.com/news/2020/03/covid19-crisis-rwanda-begins-distribution-of-essential-goods-to-citizens-affected-by-coronavirus-lockdown.html
  18. Ssuna, I., 2020. Limited COVID-19 testing? Researchers in Rwanda have an idea. Daily Herald. https://www.dailyherald.com/article/20200813/news/308139976
  19. World Food Program, 2020. Farmers in Rwanda provide food to those affected by coronavirus. https://insight.wfp.org/farmers-in-rwanda-provide-food-to-those-affected-by-coronavirus-ef4e0bf156e8
  20. World Health Organization, AFRO, 2020. Rwanda’s response to COVID 19 brings out the need to prepare and learn from practice. https://www.afro.who.int/news/rwandas-response-covid-19-brings-out-need-prepare-and-learn-practice