የመሬት አዘገጃጀት ለባቄላ

Notes to broadcasters

Save and edit this resource as a Word document.

የአዘጋጅ ማስታወሻ
ባቄላ በኢትዮጵያ ከዋና ዋና ምግቦች ጋር የሚመደብ ነው፡፡ በሌሎች አገራትም ዱኬ ባቄላ (broad bean) በመባል ይታወቃል፡፡ ይህ ጥራጥሬ ናይትሮጅን እንዲፈጠር በማድረግ ለአፈር ለምነት አስተዋፅኦ ያደርጋል፤ እንደ ስንዴ እና ጤፍ ከመሳሰሉ ዋና ዋና የምግብ ጥራጥሬዎች ጋር በማቀያየር ለማምረትም ጠቀሜታ አለው፡፡

አንዳንድ አርሶ አደሮች በበሄክታር እስከ 4800 ኪሎ ግራም ባቄላ ቢያመርቱም እንደ አገር በኢትዮጵያ በአማካይ በሄክታር 1800 ኪሎግራም ባቄላ ይመረታል፡፡ ኢትዮጵያውያን አርሶ አደሮች በቄላን ለማምረት ደለላማ፣ ቀይ፣ ወይም አሸዋማ አፈርን ይመርጣሉ፡፡ በኢትዮጵያ ባቄላን ለማምረት እንደ ፈተና ከሚጠቀሱት ችግሮች መካከል፡- ተባዮች ፣ በሽታ፣ የዘር እጥረት ፣ አረም፣የአፈር ለም አለመሆን ፣ እና ውሃ የሚያስተኛ መሬት ተጠቃሽ ናቸው፡፡

ይህ ፅሁፍ የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች ማዳበሪያ ማዘጋጀትን፤ ለመስመር ተከላ ልኬት ማድረግን፤ እና ማረስን ጨምሮ ለግብርና ወቅት መሬታቸውን ለማሰናዳት በሚያደርጉት ዝግጅት ዙሪያ ውይይት ያደርጋል፡፡ በኢትዮጵያ የተወሰኑ ባቄላ አምራች አርሶ አደሮች መሬታቸውን እስከ ሶስት ጊዜ ያርሳሉ፡፡

ፅሑፉ በተጨማሪ አንዳንድ ጊዜ በጥራጥሬ ተከላ ወቅት ጥቅም ላይ የሚውሉ የመድሀኒት ዓይነቶችንም ይጠቅሳል፡፡ እነዚህ መድሃኒቶች በተከላ ወቅት ከዘር ጋር የሚደባለቁ ምርቶች ናቸው፡፡ ወድሃኒቶቹ አስፈላጊ የአፈር ይዘቶችን በመጨመር የሰብሎችን እድገት ለማፋጠን የሚረዱ ህይወት ያላቸው ነገሮችን የያዙ ናቸው፡፡

ይህ ፅሁፍ በተግባራዊ ቃለ መጠይቅ ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ የድምፅ ተዋንያን በፅሁፉ ያሉት የተለያዩ ሚናዎችን በመያዝ በጭውውት መልኩ እንዲያቀርቡት በማድረግ ለአርሶ አደር ፕሮግራምህ እንደ አንድ ይዘት ልትመርጠው ትችላለህ፡፡ እንዲህ ካደረግክ እባክህን(ሽን) በፕሮግራሙ መጀመሪያ ላይ ድምፆቹ በትክክል ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው ሳይሆኑ የተዋንያን መሆናቸው ለአድማጮችህ ማሳወቅህን አረጋግጥ፡፡

ወይም ደግሞ ይህን ፅሁፍ ለባቄላም ሆነ ለሌሎች ሰብሎች የመሬት ዝግጅት ዙርያ የራስህን ታሪክ ለማዘጋጀት እንደ ምርምር ሰነድ ልትጠቀምበት ትችላለህ፡፡

የተሳካ የባቄላ ምርት የነበራቸው አርሶ አደሮችን በሚቀጥለው መልኩ አናግር ፡

Script

አቅራቢ:
እንኳን ወደ (የሬድዮ ፕሮግራሙ) በደህና መጡ፡፡ ዛሬ ከርዕሰ መዲናችን አዲስ አበባ ወጣ ብለን በአማራ ክልል የበቃሎ ቀበሌ ማህበረሰብን እየጎበኘን ነው፡፡ በባቄላ ዙሪያ እንነጋገራለን፡፡
ሰኔ ወር የመጀመሪያው ሳምንት ነው፡፡ የባቄላ ዘር የሚዘራበት ወቅት ደርሷል ማለት ይቻላል ፡፡ ስለዚህ ከ ዮሃንስ ከሊለ እና ከአስካለ ካሳየ ጋር መሬታቸውን እንዴት እያዘጋጁ እንደሆነ እያነጋገርኳቸው ነው ፡፡ ይህ መሬቱ እና የሚበቅለው ሰብል በየቁልቁለቱ እና ዳገቱ የተለያየ የሆነበት ገደላማ ቦታ ነው፡፡
በአንድ ተራራ ስር ካለ ጥርግያ ጎን በሚገኝ አነስተኛ የህንፃ ስብስብ አጠገብ ነኝ፡፡ እዚሁ ከአርሶ አደር ዮሃንስ እና የልማት ወኪል ከሆነው ነገሰ ወልደ ማርያም ጋር ተገናኝቻለሁ፡፡
ዮሃንስ በምን ያህል መሬት ላይ ነው ባቄላ ለማምረት እያቀድክ ያለኸው?
ዮሃንስ ከሊለ:
በአንድ ሄክታር ባቄላ ለመዝራት አቅጃለሁ፡፡ በተጨማሪም ገብስ፣ ስንዴ ፣ እና ዐተር እዘራለሁ፡፡
አቅራቢ:
አሁን በየትኛው የመሬት ዝግጅት ዓይነት ላይ ደርሰሃል?
ዮሃንስ ከሊለ:
አሁን ሁለተኛው የማረስ ስራ ላይ ነን፡፡ ሰኔ መጨረሻ ላይ ለሶስተኛ ጊዜ አርሰን ወደ ተከላ እንገባለን፡፡
አቅራቢ:
አርሶ አደሮች ባቄላን በሚዘሩበት ጊዜ ሊያስታውሱት የሚገባቸው አንድ ነገር ምንድነው?
ዮሃንስ ከሊለ:
መሬትን በአግባቡ መምረጥ አስፈላጊ ነው፡፡ በቀድሞ የምርት ዘመን ስንዴ ወይም ገብስ የተመረተበትን መሬት መምረጣችንን እርግጠኛ መሆን አለብን፡፡ መጨረሻ ላይ ዐተር የተመረተበት መሬት ከነበረ ብዙም ውጤታማ አይሆንም፡፡ ከልምድ የተማርነው ይህንን ነው፡፡
ነገሰ ወልደማርያም:
እዚህ አርሶ አደሮች የሰብል መቀያየርን እየተለማመዱ ነው፡፡ ስንዴ፣ ገብስ፣ ዐተር፣ እና ባቄላን ያቀያይራሉ፡፡ ዐተር እና ባቄላ ሲበቅሉ በቀጣይ የምርት ዘመን በቦታው ለሚበቅሉ ስንዴ እና ገብስ ጠቃሚ የሆነ ናይትሮጅንን በማምረት አፈሩን ያበለፅጋሉ፡፡ ስንዴ እና ገብስ በሚበቅልበት ወቅት ደግሞ አርሶ አደሮች ለባቄላ ጠቃሚ የሆነ ማዳበሪያ ይጨምራሉ፡፡
አቅራቢ:
አመሰግናለሁ አቶ ወልደማርያም፡፡ ዮሃንስ በዚህ መሬት መጨረሻ ላይ ያመረትከው ምንድን ነበር?

ዮሃንስ ከሊለ:
ስንዴ ዘርቼ ጥር ላይ ሰበሰብኩት፡፡ ቀጥዬ የካቲት ላይ የመጀመሪያ ዙሩን አረስኩ፡፡ ይህ ደረቅ ወቅት በመሆኑ መሬቱ ተባዮችን እንዲቀንስ ለፀሃይ ብርሃን ማጋለጥ ያስፈልገዋል፡፡
አቅራቢ:
ማሳህን ለማረስ ምን መሳሪያ እየተጠቀምክ ነው?
ዮሃንስ ከሊለ:
ስንጥቁን ማረሻ (Aybar BBM) እየተጠቀምኩ ነው፡፡ ,የዛሬ ሶስት ዓመት ነው የገዛሁት ምክንያቱም ውሃ ለሚያስተኙ መሬቶች ጥሩ ነው፡፡ የሰራተኛ ወጪ የቀንሳሉ፤ በተጨማሪም ለማረስ ቀላል እና ምቹ ነው፡፡
ቀደም ሲል አንድ ሄክታር ለማረስ ለእያንዳንዳቸው መቶ መቶ ብር እየከፈልኩኝ ሰላሳ ሰዎችን ነበር የምቀጥረው፤ አሁን ግን ለማረስ በፈለኩ ቁጥር አንድ የሚያግዘኝ ሰው ብቻ ነው የሚያስፈልገኝ፡፡
አቅራቢ:
ስንጥቁ ማረሻ ማለት ሰፋፊ ክንፎች ያሉት እና መሃል ላይ ጠባብ የውሃ ማፋሰሻ የሚፈጥር ሲሆን ውሃ ለሚተኛባቸው ማሳዎች መፍትሔ እንዲሆን ታስቦ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚመረት የማረሻ ዓይነት ነው፡፡ ስንጥቁ ማረሻ ውድ ነበር ዮሃንስ?
ዮሃንስ ከሊለ:
አይ አይመስለኝም አንድ መቶ ዘጠና ሶስት ብር ነው የፈጀብኝ፡፡
አቅራቢ:
የዘር ወቅት ወደ መድረሱ ነው ምን ዓይነት የባቄላ ዝርያዎችን ነው ለመዝራት ያቀድከው?
ዮሃንስ ከሊለ:
ባለፈው ዓመት ያስቀመጥኩት የአካባቢ ዓይነትን ነው እየዘራሁ ያለሁት፡፡ በቂ ከሌለኝ እገዛለሁ፡፡ ሆኖም ግን ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋርም ዘር እቀያየራለሁ፡፡
ነገሰ ወልደማርያም:
ብዙ አርሶአደሮች ዘር ይለዋወጣሉ፡፡ በዚያ መንገድ ዘራቸው ውሃ ለሚያስተኙ ማሳዎች ጥሩ ከሆኑ እና ፤ ነገር ግን እነሱ የሚዘሩት ውሃ በማይተኛባቸው ማሳዎች ቢሆኑ፤ ለማሳቸው ተስማሚ ከሚሆንላቸው አርሶ አደሮች ጋር ሊለዋወጡ ይችላሉ፡፡
በዚህ አካባቢ መሬቱ ከቦታ ቦታ በጣም ሊለያይ ይችላል፡፡ ተራራ ላይ ያሉ ቁራጭ መሬቶች ረባዳ ቦታ ላይ ካሉ መሬት ጋር ሲነፃፀር የተለያየ የአፈር ዓይነት ይኖራቸዋል፡፡ እዚህ አካባቢ ያሉ አርሶ አደሮችም በነዚህ የተለያዩ ቦታዎች መሬቶች አሏቸው፡፡ አንድ ዓይነት ቦታ ላይ አይደለም ማሳ ያላቸው፡፡
አቅራቢ:
ያ ስራቸውን ይበልጥ አስቸጋሪ ያደርገዋል በተለይም ደግሞ አርሶ አደሮች የእርሻ መሳሪያዎቻቸውን ከቦታ ቦታ መሸከም ስላለባቸው?
ነገሰ ወልደማርያም:
አንዳንድ ነገሮችን ብዙ የሰው ሃይል እንዲጠይቁ ያደርጋል፡፡ ሆኖም ግን የራሱ የሆነ ጥቅምም አለው፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ቦታዎች ጥሩ ዝናብ ያገኛሉ ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የአፈር ለምነታቸውም የሚለያይበት ሁኔታ ይኖራል፡፡
አቅራቢ:
ስለዚህ ዮሃንስ የመዝራት ወቅት ሲደርስ እንዴት ነው ዘሮችህን ለመዝራት ያሰብከው?
ዮሃንስ ከሊለ:
ሰፋፊ መደብ የሚያመቻችልኝ ስንጥቁን ማረሻ ስለምጠቀም ዘሮቹን በአግባቡ እዘራቸዋለሁ፡፡
አቅራቢ:
ጥሩ መልካም ዕድል ጌታዬ ፡፡
ባቀሎ ቀበሌ ወደምትገኝ ሌላ አርሶ አደር ወይዘሮ አስካለ ካሳዬ እንኳን በደህና መጣችሁ፡፡ በኢትዮጵያ በባቄላ ዙሪያ በፋና ኤፍ ኤም ለሚተላለፈው ፕሮግራም አስተዋፅኦ አድርጋችኋል፡፡ ከባቄላ አምራች አርሶ ሰደሮች ጋር ምን አይነት ምክር ነው እያካፈላችሁ ያላችሁት?
አስካለ ካሳዬ፡
መልካም ፤ ከሁሉም በፊት በባህላዊ ዘዴ ማሳችንን አንድ ጊዜ ብቻ አርሰን ነው ዘራችንን የምንዘራው፡፡ ሆኖም ግን በግብርና ቢሮ ስሰለጥን ሶስት ጊዜ ማረስ የሚሰጠውን ጥቅም ተረድቻለሁ፡፡ በሽታዎችን፣ አረሞችን፣ እና ተባዮችን ለማስወገድ ሶስት ጊዜ ደጋግሞ ማረስ አስፈላጊነቱን አውቃለሁ፡፡ በተጨማሪም ለሬድዮ ፕሮግራም አዘጋጆቹ የበሰበሰ ፍግ አዘገጃጀት ነግሬአቸዋለሁ፡፡
አቅራቢ:
በአስተራረስ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በኢትዮጵያ ጥቅም ላይ እየዋለ ያለውና ሰፊ መደብ ለመፍጠር የሚያስችለውን የማረሻ ዓይነት ትጠቀሚያለሽ?
አስካለ ካሳዬ:
አይ ባህላዊውን ነው እየተጠቀምኩ ያለሁት ነገር ግን ዮሃንስን እየሰማሁት ነው ያለሁት፤ ስንጥቁን መጠቀም ምን ያህል ቆጣቢ እንደሆነ አሳማኝ ይመስላል፡፡ ውሃ የሚያስተኛውን መሬት ላማንጣፈፍ የሚያግዙን አምስት ሰዎችን መቅጠር ያስፈልገናል ፡፡ ስለዚህ ስንጥቁን መጠቀም ብራችንን እንድንቆጥብ ሊረዳን ይችላል፡፡
አቅራቢ:
ዘርሽንም በባህላዊ መንገድ እየዘራሽ ነው?
አስካለ ካሳዬ:
አይ በዚህ ወቀት ባለችኝ ሩብ ሄክታር ማሳ ለመጀመሪያ ጊዜዬ ቢሆንም እንኳ በመስመር ለመዝራት ነው ያሰብኩት፡፡
አቅራቢ:
ባቄላን በመስመር ለመዝራት ልትጠቀም ያሰብካቸው መለኪያ መሳሪያዎች ምንድን ናቸው?
ነገሰ ወልደማርያም:
አርሶ አደሮች በመደቦች መካከል አርባ ሳንቲ ሜትር እንዲሁም በዘሮች መካከል ሃያ ሳንቲ ሜትር እያራራቁ መትከል አለባቸው፡፡
አስካለ ካሳዬ:
ይህን በቀላሉ በእጄ መለካት እችላለሁ፤ ሃያ ሳንቲ ሜትር ማለት በአውራ ጣቴ ጫፍ እና የፊት ሌባ ጣቴ መካከል ያለው ርቀት ማለት ነው፡፡ ሶስተኛ ጊዜ በምናርስበት ጊዜ ከሚያርሰው ኋላ እየተከተልኩኝ ዘሮቹን እጥላለሁ፡፡ የመጀመሪያዎቹን ዙሮች እየለካሁ ከጣልኩ በኋላ ቀጥዬ ርቀቶቹን ቀስ በቀስ መገመት እንደምችል እርግጠኛ ነኝ፡፡ በመደዳው በስተመጨረሻ ተመልሰን ሌላኛውን መደዳ ስናርስ ማረሻው ሲገፋ በመጀመሪያው መደዳ የጣልናቸው ዘሮች ላይ አፈር እየገፋ ያለብስልናል ፡፡
አቅራቢ:
አቶ ወልደማርያም ሁለቱም አዘራር ማለትም ባቄላን በባህላዊ ዘዴ በመበተን እና በመስመር መዝራት ውጤታማ ናቸው?
ነገሰ ወልደማርያም:
የተወሰኑ አርሶ አደሮች ስንጥቁን ማረሻ እየተጠቀሙ ናቸው ስለዚህም በመደዳ መዝራት አይችሉም፡፡ ሆኖም ግን ይህ ውሃ ለሚያስተኙ ማሳዎች ጥሩ አማራጭ ነው፡፡ ሌሎች አርሶ አደሮች ደግሞ በመደዳ መዝራትን እየተገበሩ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ምርት ላይ ጭማሪ ያስገኛል፡፡
አቅራቢ:
ወይዘሮ ካሳዬ እስኪ ስለ ፍግ አሰራርሽ ተጨማሪ ማብራሪያ ስጪኝ፡፡
አስካለ ካሳዬ:
በቅድሚያ አራት ሜትር በአራት ሜትር ጉድጓድ እቆፍራለሁ፡፡ በውስጡ የሰብል ተረፈምርቶች ፤ የተወሰነ የተራረፈ ድርቆሽ ፤ እና የከብቶች እበት እጨምርበታለሁ ፡፡ ከዚያም በየቀኑ ለአስራ አምስት ቀናት ውሃ አጠጣዋለሁ፡፡ በመቀጠል በየወቅቱ አደባልቀዋለሁ፡፡
አቅራቢ:
ፍግ ማዘጋጀቱንመቼ ነው የምትጀምሪው?

አስካለ ካሳዬ:
ይዘቶቹን ማጣት አልፈልግም ስለዚህ የካቲት መጨረሻ ላይ ወይም መጋቢት መጀመሪያ ላይ ነው የምጀምረው፡፡ ከዚያም ለሶስት ወራት ብቻ እቀጥልበታለሁ፡፡ በመቀጠል በሚገባ እንዲደባለቅ ከሶስተኛው የማረስ ወቅት በፊት ማሳው ላይ እበትነዋለሁ
አቅራቢ:
አቶ ወልደማርያም የተሻለ የባቄላ ምርት የሚሆን ለም አፈር እንዲኖረቸው አርሶ አደሮች ሊያዳብሩዋቸው የሚገቡዋቸው ሌሎች ልምዶችሰ አሉ?
ነገሰ ወልደማርያም:
እዚህ አካባቢ ያሉ አርሶ አደሮች የመሬታቸውን የአፈር ለምነት ለማሻሻል ማድረግ የሚችሉትን ሁሉ እያደረጉ ነው፡፡ ስንዴ እና ገብስ በሚያመርቱበት ወቅት ዩሪያ እና ኤን ፒ ኤስ የመሳሰሉ ኬሚካል ማዳበሪያዎችን ይጠቀማሉ፡፡ ኤን ፒ ኤስ የናይትሮጅን ፣ የፎስፎረስ እና የሰልፈር ቅይጥ ነው፡፡
ለባቄላ አርሶ አደሮች የብስባሽ ፍግ ፣ኤን ፒ ኤስ እየተጠቀሙ ነው፡፡ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎችም አርሶ አደሮች ለአካባቢው የአፈር ሁኔታ በሚያመች መልኩ የተቀየጠ ማዳበሪያን ይጠቀማሉ፡፡ እዚህ ያሉ አርሶ አደሮችም ስለ ቅይጡ ማዳበሪያ ሰምተዋል፤ መጠቀምም ይፈልጋሉ፡፡ ሆኖም ግን በዚህ ወቅት እዘህ የለም፡፡
እነዚህ አርሶ አደሮች በግብርና ተመኩሮዎች በሚገባ የተማሩ እና በላም ወተት ፣ በመስኖ ተክል ልማት፣ በተጨማሪም በገብስ፣ በስንዴ፣ በዐተር፣ እና በባቄላ ማቀያየር የተለያዩ የቢዝነስ ዓይነቶች ያላቸው ናቸው፡፡
አቅራቢ:
መልካም ሁላችሁንም ዕውቀታችሁን ስላካፈላችሁ አመሰግናለሁ፡፡ በባቄላው የምርት ዘመናችሁም መልካም የምርት ዘመን እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ፡፡

Acknowledgements

ምስጋና

አስተዋፅኦ አድራጊዎች፡- ካትሪን በርንሃም በፋርም ሬድዮ ኢንተርናሽናል የሪሶርስ ፕሮዳክሽን፣ ስርጭት፣ እና ግምገማ አስተባባሪ

ገምጋሚ: መለሰ ተመስገን የአይባር ኢንጂነሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ

Information sources

የመረጃ ምንጭ

ቃለ መጠይቆች:

ዮሃንስ ከሊለ፣ (አርሶ አደር) በአማራ ክልል ባቀሎ ቀበሌ ሰኔ 9 2017
አስካለ ካሳዬ  (አርሶ አደር) በአማራ ክልል ባቀሎ ቀበሌ ሰኔ 9 2017
በየነ እሸቴ  (አርሶ አደር)  በአማራ ክልል ባቀሎ ቀበሌ ሰኔ 9 2017
ነገሰ ወልደማርያም (የልማት ወኪል) በአማራ ክልል ባቀሎ ቀበሌ ሰኔ 9 2017
ተፈራ ጎንፋ ፎዱ ጎራ ቀበሌ  ኦሮሚያ ክልል ሰኔ 12, 2017
ዳዊት ጌታሁን  (የልማት ወኪል)  ፎዱ ጎራ ቀበሌ  ኦሮሚያ ክልል ሰኔ 12, 2017

ይህ ፅሁፍ በኢትዮጵያ የሰብል ምግቦች ፕሮጀክት አማካኝነት በ ቢል እና መሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን ድጋፍ የተዘጋጀ ነው፡፡